"የክልሉ መስተዳድር ምክር ቤት በ30ኛ መደበኛ ጉባኤው በቀጣይ 30 ቀናት እቅድ ስራዎች ዙሪያ በመምከር አቅጣጫ አስቀመጠ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት መስተዳድር ምክር ቤት በበይነ መረብ ባካሄደው 30ኛ መደበኛ ጉባኤው ከምርጫ ማግስት ባለው የአንድ ወር የቅድመ መንግስት ምስረታ ወቅት በሚከናወኑ የቀጣይ የአንድ ወር ስራዎች ዕቅድ ዙሪያ በመምከር ቀጣይ አቅጣጫን አስቀምጧል፡፡ በጉባኤው የክልሉን መንግስት የ2018 ያለፉ አስር ወራት አጠቃላይ ስራዎች ዕቅድ አፈፃፀም እንዲሁም እንደ ሀገር በወጥነት ለማሳካት የታለሙ ሀገራዊ የልማት ኢንሼቲቮች ታሳቢ ያደረገ የቀጣይ የአንድ ወር ስራዎች መሪ ዕቅድ ቀርቦ ሰፊ ውይይት ተደርጎበታል፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ በውይይቱ ወቅት፡- በ7ኛው ጠቅላላ ሀገራዊ ምርጫ ህዝቡ በቅድመ ምርጫና በምርጫው ሂደት ያሳየው አስደናቂ ንቁ ተሳትፎ እንዲሁም በድህረ ምርጫው የታየው ስክነትና ጨዋነት ምርጫው ፍጹም ሰላመዊ በሆነ መንገድ ዴሞክራሲያዊ ሂደቱን ጠብቆ በስኬት እንዲጠናቀቅ ማስቻሉን ገልፀው፤ ዕውቅናና ምስጋና ይገባዋል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ በቅድመ ምርጫው የተሰሩ ስራዎች ሀገራዊ ምርጫውን እጅግ ሰላማዊ፤ ነፃ፤ ፍትሃዊ፣ ታአማኒ እና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ በስኬት እንዲጠናቀቅ አስትዋፅኦ ማበርከቱን ጠቅሰው፤ የህዝቡን ሰላማዊና ጨዋነት የተሞላው ተሳትፎን ጨምሮ በሂደቱ የድርሻቸውን ለተውጡ አካላት በሙሉ ምስጋና አቅርበዋል፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ አጠቃላይ የምርጫው ውጤት በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ተገልጾ የመንግስት ምስረታ እስከሚካሄድ ምንም መዘናጋት ሳይፈጠር በምርጫው አስደናቂ አኩሪ ተግባር የፈጸመው ህዝባችንን በልማትና በመልካም አስተዳደር ስራዎች ለመካስ በልዩ ትኩረት መስራት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ ለዚህም የተጀመሩ የልማት ተግባራትን በማጠናከር ለህዝብ አዳጊ የልማት ጥያዌዎች ምላሽ መስጠት የሚያስችል በየዘርፉ የአንድ ወር እቅድ በማቀድ ለተግባራዊነቱ መረባረብ እንደሚገባ ተናግረዋል። አክለው እቅዱ በተለይ በክብር ጠ/ሚ ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፤ በየዘርፉ እምርታ ለማስመዝገብ እንደ ሀገር የተቀመጡ ሀገራዊ ግቦችን እንዲሁም በንቅናቄና በመደበኛ የሚመሩና የሚሰሩ ስራዎችን በመለየት እና ያሉ ተጨባጭ አቅሞችን ተጠቅሞ ፈጠራና ፍጥነት በታከለ አፈጻጸም ለውጤት ለማብቃት የሚያስችሉ ስልቶችን ታሳቢ ያደረገ ልሆን እንደሚገባም አስገንዝበዋል፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ የስራዎች አፈጻጸምን ለውጤት ለማብቃት በጠናካራ ድጋፍና ክትትል መደገፍ እንደሚገባም ጠቅሰው፤ በየደረጃው ያለው አመራር ከህዝብና ከመንግስት የተጣለበትን ከፍተኛ ኃላፊነት በአግባቡ በመወጣት፤ በቀሪ ጊዜያት የተሰነቁ ግቦችን ያለምንም መሸራረፍ በመፈጸምና በማስፈጸም የውጤት ዘላቂነትን ማረጋገጥ እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡ መስተዳድር ምክር ቤቱ በስብሰባው በቀጣይ 30 ቀናት ሊሳኩ የሚገቡ እና በእጥፍ ለማሳደግ መሰራት የሚገባቸውን ተግባራት በመለየት ቀጣይ አቅጣጫ ያስቀመጠ ሲሆን ከነዚህም፡- * በግብርና ልማት ዘርፍ በቀሪ የበልግና የቀጣይ የመኸር እርሻ ስራዎች ምርታማነትን የማሳደግ፤ በሌማት ትሩፋት በእጥፍ የማብዛት እንዲሁም ለአረንጓዴ አሻራ ስራዎች በትኩረት መስራት፤ * የገቢ አሰባሰብ ስራዎችን በልዩ ትኩረት በቅንጅት በመምራትና ኢኮኖሚው ከሚያመነጨው ገቢ ፍትሀዊ ግብር በመሰብሰብ የህዝብ የልማት ጥያቄዎችን በብቃት ለመመለስ የሚስችል የውስጥ አቅምን የማጠናከር ተግባራት፤ * አገልግሎት አሰጣጥ የማዘመን ስራዎችን የማጠናከር በተለይም በዲላ እና በአርባ ምንጭ ከተሞች የተጀመሩ የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ማዕከላት ፈጥኖ በማጠናቀቅ ወደ አገልግሎት ማስገባት፤ እንዲሁም በሁሉም የከተማ አስተዳደሮች እንደየከተሞች ነባራዊ ሁኔታ በማስፋት በክልሉ የአገልግሎት አሰጣጥን በቴክኖሎጂ የተደገፈ፤ ፈጣንና ቀልጣፋ የማድረግ ተግባራት፤ * የተጀመሩ የከተሞች የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራዎች በማጠናከር ከዳር የማድረስ እንዲሁም የገጠር ኮሪደር ልማትን በሁሉም የገጠር ቀበሌዎች በመጀመር የታለመውን የገጠር ሽግግር ለማሳካት እና የአርሶ አደሩን ህይወት በማሻሻል ተጠቃሚነቱን ለማረጋገጥ በትኩረት መስራት፤ * ለዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ቁልፍ የሆኑ የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ እና የ 5 ሚሊዮን የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ግቦች ሙሉ በሙሉ ለማሳካት በልዩ ትኩረት መስራት፤ *በቱሪዝም ዘርፍ የክልሉን እምቅ አቅም መጠቀም በሚያስችል አግባብ በሁሉም ዞን እና ሪጂዮ ፖሊስ ከተሞች አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻ ማዕከላትን መለየትና ማልማት፣ በኢንዱስትሪ ልማት ዘርፍ የተጀመሩ ተግባራትን ማጠናከር እንዲሁም አዳዲስ ኢንዱስትሪዎችን ለመጀመር የሚስችል ስራዎችን መስራት፤ በአጠቃላይ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት በማረጋገጥ ከተረጂነት የሚያልቅቁ ተግባራት፤ የኑሮ ውድነት ጫናን የመቀነስና ገበያ የማረጋጋት፤ የአደጋ ስጋት ተግባራት እንዲሁም የክልሉን ሰላም ለማፅናት የፀጥታ ስራዎች የማጠናከር ቀጣይ አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ መደበኛ ስብሰባውን አጠናቋል።"